ኦሮምኛ የፌደራል መንግስት ሁለተኛ የስራ ቋንቋ ከመሆኑ በፊት መሟላት ያለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች

በሰለሞን ነጋሽ

1 ናዝሬት ከተማ ተወልደው ያደጉ አማርኛ ተናጋሪ ወጣቶች ኦሮምኛ መናገር ስለማይችሉ ተወልደው ባደጉበት ከተማ ስራ ማግኘት አልቻሉም። ስራውን የተቆጣጠሩት ከሌላ ቦታ የመጡ ኦሮምኛ ተናጋሪዎች ናቸው።  አማርኛ ተናጋሪዎቹ ስራ ፍለጋ ከተማዋን ጥለው አዲስ አበባና ሌሎች ከተሞች ለመሔድ ይገደዳሉ። በርካቶች ተወልደው ካደጉበትና ለፍተው ካቀኗት ከተማ ያለፍላጎታቸው በዘዴ ተባርረዋል። አሁንም እየተባረሩ ነው። ይህ የሆነ አማርኛ በነዚህ ከተሞች የስራ ቋንቋ ባለመሆኑ ነው! አማራና አማርኛ ተናጋሪ በብዛት በሚኖርባቸው ከተሞች አማርኛ የስራ ቋንቋ ሳይሆን ኦሮምኛ ከኦሮሚያ ውጭ የስራ ቋንቋ የሚሆንበት ምክንያት ለማንም ጤነኛ ሰው ሊገባው የሚችል ነገር አይደለም። አመክንዮው የተፋለሰ ነው። ባስ ሲልም ስግብግብነት ነው። What’s mine is mine and what’s yours is ours እንደሚሉት!

2 በናዝሬት፣ በደብረዘይትና የመሳሰሉ ከተሞች ለአንድ ወገን አመርቂ ውጤት ሲያስገኝ፣ በአዲስ አበባም ያንኑ ጌም ለመድገም አኮብኩበዋል። ኢንጅነር ታከለ ኡማ በህገወጥ መንገድ የአዲስ አበባ ከንቲባ ሆኖ ከተሾመ ወዲህ ብዙ አነጋጋሪ ነገሮች አዲስ ላይ ተሰርተዋል። በስፋት ኦሮምኛ ተናጋሪ ከገጠር እያመጡ አስፍረዋል። ከዚህ ጋር በተያያዘ በሚመስል መልኩ የመሬት ዝርፊያ መጧጧፉን የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽነር በአንድ ወቅት ለሚድያ ተናግረው ነበር። በህገወጥ መንገድ የከተማዋ ኗሪ ላልሆነ መታወቂያ ማደል፣ የከተማዋ ኗሪ ለሆነው መከልከል፣ ባስ ሲልም ቤታቸውን እያፈረሱ ዶክሜንታቸውን ማቃጠል፣ ታከለ ከመጣ ጀምሮ ሲከናወኑ ካየናቸው አደገኛና አስነዋሪ ድርጊቶች መካከል በጥቂቱ የሚጠቀሱ ናቸው። በዚህ ሁኔታ ከቀጠለ በአዲስ አበባ እጣ ፈንታ ወሳኙ በኦሮሞ የሚመራው መንግስት፣ ህገወጡ ከንቲባና ጀሌዎቹ እንደዚሁም ዛሬ በህገወጥ መንገድ እያሰፈሩና መታወቂያ እያደሏቸው ያሉት የገጠር ካድሬዎች ይሆናሉ ማለት ነው። ህገወጡ ከንቲባ ተነስቶ ይህ አፓርታይዳዊ የሆነና ህገወጥ አካሔድ ቶሎ ካልተገታ፣ ኦሮምኛን በአዲስ አበባ የስራ ቋንቋ ማድረግ ፈጽሞ የማይታሰብ ነው!

3 ወሳኙ የአዲስ አበባ ህዝብ የሚያስተዳድረውን ምክር ቤትና ከንቲባ መምረጥ እንዳለበት ሁሉ ኦሮምኛ እንደ ሁለተኛ የስራ ቋንቋ ስለማስፈለግና አለማስፈለጉም ድምጹን ሊሰጥበት ይገባል። እንደዚህ አይነት ጉዳዮች ከላይ የሚጫኑ መሆን በፍጹም የለባቸውም! ከተማዋ የኗሪው ህዝብ ከተማ እንደመሆኗ መጠን (ካስፈለገም ራሱን የቻለ ክልል መሆን እንደሚችል ሳንዘነጋ!) የሚበጅና የማይበጅ ነገር የመምረጥና የመወስን ስልጣን ያለው ኗሪው ህዝቧ ነው። ከተማዋን በሚመለከት ትላልቅ ውሳኔዎች ከከተማዋ ውጭ የሚኖሩና በብሔራቸው የተደራጁ ካድሬዎች ማስተላለፍና ማጽደቅ ይቅርና አጀንዳ ማድረግ የሚችሉበት ምንም ዓይነት ተፈጥሯዊም ይሁን መንግስታዊ  ህግ የለም። ስለዚህ ህዝብ ሊያምንበትና ይሁንታውን በድምጹ ሊያሳውቅ ግድ ይላል።

ህዝቡ ሲወስን ግምት ውስጥ ማስገባት ያለበት ነገር አለ። የጋራ ጥቅሙን ያስከብርለታል አያስከብርለትም? የአጭርና የረዥም ግዜ እንድምታው ምንድን ነው? በውስጡና በዙሪያው ካሉ ዜጎች ጋር በእኩልነትና በፍትሃዊነት እንዲኖር ይረዳዋል? አብሮ የሚያኗኑር ነው? ለአንድ ብሔር የበላይነትና ለግጭት አይዳርግም? ልዩ ጥቅም ከሚሉት ቅዠት ጋር የተቆራኘ ነው? ወዘተ የሚሉትን ጥያቄዎች በደንብ እያገናዘበ መመለስ አለበት። ለመነሻ እኔ የሚታዩኝን 3 ትላልቅ ነጥቦች አካፍላችኋለሁ።

1 ይህ ጉዳይ ልዩ ጥቅም ለሚባለው ኮተት አንዱ ማስፈጸሚያ መንገድ ነው። ኦሮሚያ ከአዲስ አበባ ምን ስለሆነች ልዩ ጥቅም ትፈልጋለች? ከተማዋ ስትሰፋ ከመሬቱ ለምታፈናቅለው ገበሬ በቂ ካሳና ማቋቋሚያ መስጠት አለባት ከሆነ የግድ ነውና ያስማማናል።  ገበሬው በከተማዋ ውስጥ ለመኖር ፍላጎቱ ከሆነ ጣጣውን አዲስ አበባ ትጨርሰዋለች። ገበሬው የኑሮ ዘይቤውን ሳይቀይር በግብርና እየተዳደረ መኖር የሚፈልግ ከሆነ፣ በቅድሚያ አዲስ አበባ ለወሰደችበት መሬት ለገበሬው በቂ ካሳ ትከፍላለች፣ በመቀጠል በፈለገው ክልል ተለዋጭ መሬት ይሰጠዋል። ጉዳዩ በዚህ ይቋጫል።

አዲስ አበባ ስትሰፋ ከኦሮሚያም ከአማራም ከምኑም እየፈለሱ በሚመጡ ዜጎች እንደመሆኑ መጠን፣ ገበሬው በኦሮሚያ ክልል መኖር የሚፈልግ ከሆነ ተለዋጭ መሬቱን ኦሮሚያ የመስጠት ግዴታ አለባት። ከኦሮሚያ እየፈለሱ አዲስ አበባ የሚከትሙ ኦሮሞዎች መሬታቸውን ተሸክመው አይመጡም። ያ መሬት ሌሎች ሲፈናቀሉ በካሳም ይሁን በልዋጭ መንገድ ሊሰጣቸው ይገባል። በዚህ ስሌት ኦሮሚያ የምታተርፈው እንጂ የምታጣው ስንዝር መሬት የላትም። ምክንያቱም በአዲስ ዙሪያ ያሉ ጥቂቶች ቢፈናቀሉም በሺዎች የሚቆጠሩ ኦሮሞዎች በየዓመቱ እየፈለሱ አዲስ አበባ ቤታቸውን ያደርጋሉና ነው። አዲስ አበባ ፈልሰው ለሚገቡት ኦሮሞዎች ቤታቸው እንደሆነች ሁሉ፣ ኦሮሚያም ተፈናቅለው ለሚመጡባት ገበሬዎች ቤታቸው ልትሆን ይገባል። አለበለዚያ ወደ አንድ አቅጣጫ ብቻ የሚፈልስ ሰፋሪ ሊኖር አይችልም። አዲስ አበባም ከኦሮሚያ ፈልሶ ለሚመጣው በሯን ዝግ ማድረግ ትችላለች! 

2 ኦሮምኛ በአዲስ አበባ የስራ ቋንቋ ሲሆን የመንግስት መስሪያ ቤቶች በኦሮሞ ቁጥጥር ስር ይወድቃሉ። እኩልነትና ፍትሕ አይኖርም። በመጨረሻም አዲስ አበባ እንደነናዝሬት በዝግታ ትሞታለች። አንድ ምሳሌ ልጥቀስ። የስራ እድል። ኦሮምኛ ተናጋሪው በአማርኛና በኦሮምኛ ስራ መቀጠር ይችላል። አማርኛ ተናጋሪው መቀጠር የሚችለው በአማርኛ ብቻ ነው። የስራ ቋንቋው ኦሮምኛ ከሆነ ባይ ዴፎልት በሩ ተቆልፎበታል። ኦሮሞው በኦሮምኛ ብቻ የሚወጣውን ማስታወቂያ ለሌሎች ዝግ አድርጎና ለራሱ ብቻ አድርጎ፣ በአማርኛ የሚወጣው የስራ ማስታወቂያ ላይ ደግሞ ከሌላው እኩል መወዳደር ይችላል። (በድጋሚ What’s mine is mine and what’s yours is ours!) በዚህ ሁኔታ እኩልነትና ፍትሕ አፈርድሜ ትግጣለች። ፍትሕና እኩልነት የተጓደለበት ሲስተም ደግሞ መጨረሻው አንዱን የበላይ ሌላውን የበታች ማድረግ ነው።

አዲስ አበባ የሚኖር አማርኛ የማይችል ኦሮሞ የለም። ካለም በጣም ትንሽ ነው።በቁጥር ከነናዝሬት ተፈናቅሎ ከሚመጣው አማርኛ ተናጋሪ አይበልጥም። ነገር ግን አማርኛ እየቻሉ በኦሮምኛ አገልግሎት ማግኘት የሚፈልጉ ይኖራሉ። በቁጥር በርካታ እንደሚሆኑም እገምታለሁ። አላማቸው ከላይ የተጠቀሰው ነው። የራሳቸውን ዘግተው የሌላውን መቀራመት! ይህ ቅዠት ነው። መቼም ቢሆን አይሆንም።

ከዚህ በተጨማሪ አዲስ አበባ የሚኖረው ጉራጌም ትግሬም ሶማሌም ወላይታም ሌላውም እንዲሁ በቋንቋው አገልግሎት እንዲሰጠው ይፈልጋል። ለአንዱ ፈቅዶ ለሌላው መከልከል አይቻልም። ሁሉንም ለመፍቀድና ወደ ተግባር ለመቀየር ደግሞ የአዲስ አበባ ግብር ከፋይ ማህበረሰብ አፎርድ ማድረግ አይችልም። ለዚህም ነው ደጋግሜ በድምጹ ውሳኔውን መስጠት ያለበት ይህ ህዝብ ብቻ ነው የምለው።

ኦሮምኛ

3 ኦሮምኛ ከክልሉ ውጭ የስራ ቋንቋ የሚሆን ከሆነ፣ መጀመሪያ በፋፋ ልዋጭ በተገዛ የላቲን ፊደል መጠቀሙን አቁሞ በግዕዝ ፊደላት መጻፍ ይኖርበታል። ማንነቱንና ሉአላዊነቱን በከባድ መስዋእትነት እያስጠበቀ ከትውልድ ወደ ትውልድ ለምዕተ ዓመታት ሲያስተላልፍ የኖረ ጀግና ህዝብ ዛሬ በዚህ የረቀቀ በሚመስል ነገር ግን የጅሎች ወጥመድ ስር ይወድቃል ብዬ አላምንም። ኢትዮጵያውያን ቋንቋንችን ቢለያይም በግዕዝ መጻፋችን አንድ ያደርገናል! ኤርትራ እንኳን ስትገነጠል ግዕዝን ይዛ ነው። ኢትዮጵያውያን የተራቀቁበትን፣ የታሪክ አሻራቸውን ያኖሩበትን፣ የማንነታችን አንዱ ውብ መገለጫ የሆነውን ግዕዝ ፊደላችን ተገፍትሮ በባዕድ ፊደላት የሚጻፍ ቋንቋ እንደሁለተኛ የስራ ቋንቋ የምንቀበልበት ምንም ምክንያት ሊኖር አይችልም!!

ልብ በሉ ኦሮሚያ ውስጥ የሚኖሩ ዜጎች በፈለጉበት መንገድ ይጻፉ፣ የምቃወመው ነገር አይደለም። ኗሪው ህዝብ ካመነበት አመነበት ነው። ነገር ግን ከክልሉ ውጭ የስራ ቋንቋ ይሁን ሲባል ኦሮሞ ያልሆነ ከዚህ አንጻር፣ ማለትም ታሪኩንና እሴቱን ከማስጠበቅ አንጻር፣ ተመልክቶ ውሳኔ መስጠት እንደሚገባው እየጠቆምኩ ነው። ባለመታደላቸው  ለኦሮሞ ልሂቃን ኢትዮጵያዊነት ጽያፍ ነው። የፕሮፓጋንዳ ሰለባና የነሮማን ፕሮቻስካ ራዕይ አስፈጻሚዎች ናቸውና ረቂቅነቱ አይታያቸውም። ካባውን አይደርቡትም፣ ያፍሩበታል። ሉአላዊነቱን ሳያስደፍር፣ ባህሉንና ማንነቱን ሳይከልስ ለሺዎች አመታት ሳይደፈር መኖሩን ይሸማቀቁበታል። ቅኝ ተገዢነት ይናፍቃቸዋል። የባዕድ ፊደል ያምራቸዋል። ይህን የስነልቦና ቀውስ ከራሳቸው አልፎ የኦሮሞ ህዝብ ላይም ተጭነውታል። ያሳዝናል። ነገር ግን ሌላው ጋ እንዲዛመት መቼም ቢሆን አንፈቅድም። መቆም አለበት!!

****

አመሰግናለሁ! ጥያቄና አስተያየት ካላችሁ ከታች ሀሳብ መስጫው ላይ ወይም እዚህ ላይ ጻፉልኝ።

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *