, , , , ,

የኢትዮጵያ ጉዞ ወዴት? የኋላው ከሌለ የለም የፊቱ! (ክፍል 1)

የኢትዮጵያ እና የአውሮፓ ንፅፅር

Why Nations Fail በተሰኘው መፅሃፋቸው የMIT ና የHarvard ፕሮፌሰሮች የሆኑት Daron Acemoglu ና James A. Robinson (ከዚህ ብኋላ A&R) ኢትዮጵያን ከአክሱም ዘመነ መንግስት አንስቶ እስከ 16ኛው ክፍለዘመን ድረስ ከአውሮፓ አገራት ጋር ተነፃፃሪ የስልጣኔ እርከን ላይ ትገኝ እንደነበር ይገልፃሉ። ለምሳሌ አክሱም ከሮም ስልጣኔ ጋር ተነፃፃሪ (comparable) እንደነበረች ሲያትቱ በኢኮኖሚያዊ ተቋማቶቿ ብቻ ሳይሆን በፖለቲካ ርዕዮተ ዓለሟም ጭምር እንደሆነ ይገልፃሉ። ባህር ተሻጋሮ የንግድ ልውውጥ ማካሄድ፡ ገንዘብ መጠቀም፡ ትላልቅ ሃወልቶችንና መንገዶችን መገንባት እንዲህውም እርሻ ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚ ማራመድ የሚጋሯቸው እንቅስቃሴዎች ነበሩ። የሁለቱም አገራት ነገስታት በተቀራራቢ ጊዜ ክርስትና የተቀበሉ መሆናቸውና በተመሳሳይ ጊዜም ስልጣኔያቸው መዳከሙ ከሚያመሳስሏቸው በርካታ ነገሮች መካከል እንደሆኑ ይጠቅሳሉ።

አክሱም ስልጣኔ ከተዳከመ ብኋላ የአገሪቱ ዕጣ ፈንታ ከሌላው ዓለም ተነጥሎ ተራራ ላይ በመስፈር በዝባዥ የሆነ ፍፁማዊ ስርዓት (absolutist empire) መፍጠር ሆነ። በተመሳሳይ ሁኔታ ከሮም ስልጣኔ መፍረስ ብኋላ በአውሮፓም (ለምሳሌ በኢንግሊዝ) ተመሳሳይ ስርዓት ነገሰ። በኢትዮጵያ በ13ኛው ክ/ዘመን ገደማ (ምናልባትም ቀደም ብሎ) የጉልት ስርዓት ሲፈጠር፡ በአውሮፓም (በተለይ በኢንግሊዝ) ተመሳሳይ ስርዓት (Fuedal Land Tenure) ተፈጥሮ ነበር።  ይህ ስርዓት በሁሉም አገራት ባላባቶቹን እያጎለበተ ተራውን ገበሬ አቅም ቢያሳጣውም በተለይ በኢትዮጵያ በጣም አስከፊና ለረዥም ጊዜ ተገዳዳሪ ሳይገኝለት የዘለቀ ስርዓት እንደነበር ከበርካታ ጎብኚዎች ድርሳናት ማስረጃ ማግኘት ይቻላል። ለምሳሌ ፖርቹጋላዊ ሚስዮናዊ Alvares በ1520ዎቹ የጻፈው ምስክርነት እስከ መሬት ላራሹ ዘመን ድረስ የነበረውን የአገሪቱን እውነታ የሚያንፀባርቅ ነበር፡

“There would be much more fruit and tillage if the great men did not ill-treat the people. … Often one man plows the soil, another sows it and another reaps…. There is no one who takes care of the land he enjoys; not even any one to plant a tree because he knows that he who plants it very rarely gathers the fruit. For the king, however, it is useful that they should be so dependent upon him.”

ለረዥም ጊዜ በአገሪቱ ፖለቲካ የበላይነት ይዛ የቆየችው የቤተ ክርስቲያን ሚና ደግሞ በመንግስቱ ላይ የማያምፅ “ተመስገን ባይ ህዝብ” መፍጠር ሆነ። በፖለቲካው ረገድ ነገስታቱ መንበረ ስልጣናቸውን ከሰለሞናዊው ስርወ መንግስት ጋር በማቆራኘት በእግዜር የተመረጡና በካህን የተቀቡ መሆናቸውን በህዝቡ አእምሮ ውስጥ ማስረፃቸው ህዝብ በአመፅ እንዳይነሳባቸው እድርጓል። በሌላው አለም ላይ (ለምሳሌ በ16ኛው ክፍለዘመን በኢንግሊዝ) እንደታየው ህዝብ በፍፁማዊው አገዛዝ ላይ በማመፅ ነፃነትን ለማስከበር ንቃተ ህሊናው እልዳበረም ነበር። የነዚህ ጥምር ውጤት ደግሞ የ18ኛው ክፈለዘመን የታሪክ አጥኚ Edward Gibbon እንዳለው ከሌላው ዓለም በመነጠል ለዘመናት ጥልቅ እንቅልፍ ውስጥ ገብቶ መርረሳት ሆነ፡

“Encompassed on all sides by the enemies of their religion, the Ethiopians slept near a thousand years, forgetful of the world by whom they were forgotten.”

በየጊዜው የውጭ ወራሪ ኃይል ወይም አልፎ አልፎ የውስጥ ተስፋፊ ሃይል ሲያጋጥም ያንን ለመመከት በሚጎሸም የክተት ነጋሪት ከዕንቅልፉ ካልነቃ በስተቀር ተራራ ላይ የሰፈረው ህዝብ የራሱ የፖለቲካ አጀንዳ ወይም የስልጣኔ ራዕይ ኖሮት ራሱን ከበዝባዥ ስርዓት ነፃ ለማውጣት ወይም ለመስፋፋት አሊያም ወጥ ማህበረሰብ ለመፍጠር ሲሞክር አልተስተዋለም። ባጭሩ በመካከለኛው ዘመን እኩዮቹ የነበሩት የአውሮፓ አገራት የተከተሉትን መንገድ ሳይከተል ቀረ።

(ወደ ቀጣዩ ገፅ ተዛውሯል)

0 replies

Leave a Reply

Want to join the discussion?
Feel free to contribute!

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *